Sunday, July 26, 2015

መንፈሳዊ መታለል በነቢያት በኩል


የእግዚአብሔር ህዝብ በነቢያትበኩል ለዘመናት ሲታለል ኖሮአል፡፡ እውነተኛነቢያት እንዳሉ የሳቱ ነቢያትም አሉ፡፡
ነቢያት ከቀናው መንገድ ወጥተው ወደ ስህተት ሲገቡ ህዝብንም ያስታሉ፡፡ በዘመናት መካከል የሰዎችን ልብ ገዝቶ የመያዝ አቅም ከነበራቸው መሪዎች ውስጥ ነቢያት በስህተትም ይሁን በቀና መንገድ ግንባር ቀደም ናቸው ቢባል እብለት አይሆንም፡፡በተለይም በዚህ ረገድ ሐሰተኛ ነቢያት ስኬታማ ነበሩ፣ዛሬም ናቸው (ሉቃ 6፡26)፡፡ በነቢያት በኩልም ሆነ እንዲሁ የእግዚአብሔር ቃል ዕውቀት በነበራቸው ሰዎች ዙሪያ የተከሰተውን መንፈሳዊ/ሰይጣናዊ መታለል በተመለከተ ከመፅሐፍ ቅዱስ የሚከተሉትን ምሳሌዎች በአስተዋፅኦ መልክ እንመለከታለን፡፡
ሀ/ ኤልፋዝ
ሰይጣን ኢዮብን በሚስቱ ሳይቀር ፈትኖ ሳይሳካለት በጓደኞቹ በኩል መጣ፡፡ ኤልፋዝ ከእነርሱ አንዱ ነው፡፡መንፈሳዊ በሚመስል ምክር ኢዮብ በኃጢአቱ ምክንያት ይህ ሁሉ እንደደረሰበት ያምን ዘንድ ይዘበዝበዋል ኢዮ 4፡7-9፤5፡17 በተለይ ኢዮ 5፡27፡፡
ይህ መልዕክት ከመንፈሳዊው ዓለም ለኤልፋዝ መጥቶለታል ኢዮ4፡12-21፤ በመጨረሻ ለዚህ አገልግሎቱ ንስሐ ይገባ ዘንድ በእግዚአብሔር ተገስጾአል ኢዮ 42፡7-9፡፡ ልብ ማለት የሚገባን ይህ ሰው ምክሩን የተቀበለው ከሰይጣን መሆኑን ነው፡፡
ለ/ የሚካ ቤት ሌዋዊ
መሳ18፡5-6
ከአገልግሎት ኮብልሎ ጣኦት እያገለገለ ነው መሳ 17፤የአህዛብ አማልክት (ጣኦታት) ደግሞ አጋንንት ናቸው፡፡
ግን ለዳን ነገድ ሰዎች የተፈፀመ መልዕክት አምጥቶአል፣ በእግዚአብሔር ስም፡፡
አህዛብ ለተለየ ጉዳይ (የእግዚአብሔርን ህዝብ ከእጃቸው ለማዳን ሲል) በእግዚአብሔር ህልም የተሰጣቸው፣ራዕይ ያዩበት አጋጣሚ ነበር፡፡ አቤሜሌክ (የጌራራ ንጉስ) ስለአብርሀም፣ ስለጌድዎን የምድያም ወታደር ያየው ህልም እና በለዓም ይጠቀሳሉ፡፡
ግን ጣኦትን የሚያገለግል ሌዋዊ መልዕክቱን ከየት አመጣው ብሎ መመርመርአግባብነት አለው፡፡
የዳን ሰዎች የያዙዋት ምድርም ለኢያሱ ከተነገረው ካርታ ውጭ ናትና እግዚአብሔር ራሱን አይቃረንም፡፡
ሐ/ የአክአብ ዘመን ነቢያት
1 ነገ 22፡5-23
እነዚህ ይስቱ ዘንድ እግዚአብሔር አሳልፎ ለሰይጣን የሰጣቸው ነቢያት ናቸው፡፡ “ወጥቶ በሬማት ዘገለዓድ ይወድቅ ዘንድ አክአብን የሚያሳስት ማን ነው?” በሚል ነው እግዚአብሔር ለፍርድ የተነሳው፡፡
እሺ ባይል እንጂ እግዚአብሔር በብቸኛው ነብይ በሚክያስ እውነተኛውን ትንቢትም አምጥቶለት ነበር፡- “እስራኤል ሁሉ ጠባቂ እንደሌላቸው በጎች በተራሮች ላይ ተበትነው አየሁ፤እግዚአብሔርም፡- ለእነዚህ ጌታ ያላቸውም እያንዳንዱም በሰላም ወደ ቤቱ ይመለስ አለ” ቁ.17፡፡
መመርመር የአክአብ ፈንታ ነበር፡፡ በድምፅብልጫ ከሆነ ውሸት እና እውነት 400ለ1 ነበሩ
ኢዮሳፍጥ ተጠራጥሮ፡- “እንጠይቀው ዘንድ ሌላ የእግዚአብሔር ነቢይ በዚህ አይገኝምን?” እንዳለው ማለት ኃጢአት ሳይሆን ብስለት ነው ቁ.7
መ/ የኤርምያስ እና የሕዝቅኤል ዘመን ነቢያት
ኤር 23፡13-32
የሰማርያ ነቢያት በበአል ስም ትንቢት ይናገራሉ (ቁ.13)፤በአል ጣኦት ነው፡፡ ከበስተጀርባው ግን አጋንንት አሉ፡፡
የኢየሩሳሌም ነቢያት ኃጢአት ይሰራሉ፤ከልባቸው አውጥተው በውሸት ይናገራሉ ቁ.14-17፤የጌታን ምክር አይሰሙም ቁ.18
ስለዚህ ገለባን ከስንዴ ለይቶ መመገብ የእኛ ፈንታ ነው ቁ.25-29
የሕዝቅኤል ዘመን ነብያትን በሁለት መመደብ ይቻላል፡-
1. ስለ ጭብጥ ገብስና ቁራሽ እንጀራ የሚተነብዩ
ሴቶች ነበሩ ሕዝ 13፡17-23
በዚህ ዘመን የሚያገኙትን ጥቅም (ገንዘብ)፣ስጦታ አይተው ሰላም በሌለበት ሰላም የሚሉትን አይነት ናቸው፡፡
2. እግዚአብሔር ለአይምሮአቸው አሳልፎ የሰጣቸው
ያሳታቸው ናቸው ሕዝ 14
ጣኦት በልቡ ለያዘ ህዝብ ሰላምን፤በረከትና እረፍትን የሚተነብዩ ናቸው
ጌታ ለሽማግሌዎቹ የላከው መልዕክት የማይለወጥ ነበር፣በኤርምያስ ለ40 ዓመታ እንደተተነበየው ያው ነበር፡- “እግዚአብሔር እንደዚህ ይላል፡- ንስሐ ግቡ” ቁ.6
ከዚህ ውጪ ኖህ (ታላቁ የንስሐ ሰው)፣ኢዮብ (ንፁሁ) እና ዳንኤልን በኮንፍረንሳችሁ ብትጋብዙ እንኳን ለውጥ የለም እነሱም ያለነብሳቸው ማንንም አያድኑም የሚል ነው፡፡
ሠ/ አሳች መንፈስና የጌታ ኢየሱስ ፈተናዎች
ማቴ 4፡1-11
“እነዚህን ድንጋዮች እንጀራ እንዲሆኑ በል” ቁ.3 በራበው ጊዜ፡፡
ፀጋን ለጊዜያዊ ፍላጎታችን መገልገያ ለማዋል መፈተንን ያመለክታል፡፡
ቃል ጠቅሶ ለአጓጉል ተአምራት (ከመቅደስ ጫፍ ራስን እንዲወረውር እና እንዲተርፍ) ማነሳሳት ቁ.5-7
ቃሉን abuse ለማድረግ (አለአግባብ እንድንጠቀም) ማነሳሳትና ማሳት፣ከተፃፈበትመንፈስወጥተን እንድንተረጉመው በማድረግ ከእግዚአብሔር ጋር ማጣላት
ከሰገደለት “የዓለምን መንግስታት ክብራቸውንም አሳይቶ”እንደሚሰጠው ተስፋ ገባለት ቁ.8-9
ጌታ መንግስተ ሰማያትን ሲሰብክ፣ሰይጣን ሁሌ መንግስተ ዓለምንና ክብሯን በመስበክ ሊያታልለን፣ ሊያስተን ይጥራል ሮሜ 4፡17፤ፊልጵ 3፡18-21፤ቆላ 3፡1-4፤የቆላስያስ ሰዎች በዚያን ዘመን ስጋን በመጨቆን ያምኑ ነበር ቆላ2፡16-23፡፡ የዚህ ዘመን የብልፅግና ወንጌል ደግሞ ተቃራኒውን ጽንፍ ይዞአል ግን ልናተኩር የሚገባን በቆላ 3፡12-17 መሰረት በላይ ኢየሱስ ባለበት ባለው ላይ ነው፡፡ያም ሰማያዊ ብልፅግና ነው፡

ረ/ አሳች መንፈስና የትክክለኛ ተአምራት ፈተናዎች ዘዳ 13፡1-5
• እግዚአብሔር ህዝቡ ቃሉን ያከብር ወይስ አያከብር እንደሆነ ለመፈተን እንደቃሉ ያልሆኑ እውነተኛ ምልክትና ተአምራት ሊልክ ይችላል፡፡ ተፈትኖ ለማለፍ ቃሉን የሙጥኝ ብለን ነቢዩን ወይም ህልም አላሚውን እንቢ ማለት የእኛ ፈንታ ነው፡፡ የብሉይ ዘመን ጣኦታት ተቀርፀው የተሰሩ የአማልክት ምስሎች ናቸው፡፡ የአዲስ ኪዳኖቹየእኛ ጣኦታት ደግሞ ገንዘብ፣ሆድ/ምድራዊነትና ዓለማዊነት ናቸው፡፡ ይህንን የመጀመሪያ አድርጎ በልባችን የሚስል የትኛውም አገልጋይ ድንቅና ተአምራት ቢከተለው ልንቀበለው አይገባም፡፡
ሰ/ አሳችመንፈስና እንክርዳዶች
በማቴ7 ቁ.15 መሰረት ሐሰተኛ ነቢያት፣የበግ ለምድ የለበሱ እንጂ በግ አይደሉም፡፡አላማቸው በጎችን መብላት ነው (ጥቅም)፡፡ በቁ.16-10 መሰረት መልካም ፍሬ የላቸውም፤ከባህርያቸውም ፍሬ ሰጪ ዛፎች አይደሉም፡፡
• እንክርዳዶች ናቸው “እንክርዳዱም የክፉው ልጆች ናቸው፡፡ የዘራውም ጠላት ዲያቢሎስ ነው” ማቴ 13፡39፡፡
• ስለ እንክርዳዱ “ሰዎቹ ሲተኙ ግን ጠላቱ መጣና በስንዴው መካከል እንክርዳዱን ዘርቶ ሄደ፡፡ ስንዴውም በበቀለና በአፈራ ጊዜ እንክርዳዱ ደግሞ ያን ጊዜ ታየ፡፡ የባለቤቱም ባሮች ቀርበው “ጌታ ሆይ መልካምን ዘር በእርሻህ ዘርተህ አልነበረምን? እንክርዳዴንስ ከወዴት አገኘ አሉት፡፡ እርሱም፡- ጠላት ይህንን አደረገ አላቸው” ቁ.25-28፡፡ ስራው የጠላት ነው፡፡ ጠላት ደግሞ አመሳስሎ ስለሰራው ስንዴው በቅሎ ባፈራ ጊዜ ነው እንክርዳዱ የታየው (ቁ.26)፡፡ የእግዚአብሔር ህዝብ ህይወቱ ፍሬ አልባ በሚሆንበት ዘመን እንክርዳዶችን መለየት ፈፅሞ አይቻልም፡፡
• ከዚህ ውጭ መከር ሳይደርስ እንክርዳድን ለመልቀም መሞከር ስንዴውን አብሮ ማጥፋትን ሊያስከትል ይችላል ቁ. 29-30፡፡
• የሆነው ሆኖ እስከመጨረሻው መከር (የዓለም መጨረሻ) ከመጠበቅ ከወዲሁ ፍሬ ማፍራት ይጠበቅብናል፡፡ ያኔ እንክርዳዱ ራሱ ያለ ፍሬ ቆሞ ይታያል፡፡
• ስለመጨረሻው ዘመን ጌታ፡- “ማንም እንዳያስታችሁ ተጠንቀቁ፡፡ ብዙዎች፡- እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉና፤ብዙዎችንም ያስታሉ፡፡ በዚያን ጊዜ ማንም፡- እነሆ ክርስቶስ ከዚህ አለ ወይም፡- ከዚያ አለ ቢላችሁ አትመኑሐሰተኞች ክርስቶስችና ሐሰተኞች ነቢያት ይነሳሉና ቢቻላቸውስ የተመረጡትን እንኩዋ እስኪያስቱ ታላላቅ ምልክትና ድንቅ ያሳያሉ” ብሎናል ማቴ 24፡4-5፤23-24፡፡
ማጠቃለያ
ይህ ዘመን ህዝብ ነቢያትን እየተከተለ ቃሉን የጣለበት ዘመን ነው፣ ነቢያቱ ቃሉን አያስተምሩትምና፡፡ የልባቸውን የመልካም ምኞት መግለጫ መፈክር ይጮኹለታል፡፡ ህዝቡም በስካር ለምድራዊ ስኬትና ብልጽግና ይሁንታውን በአሜንታ ሁካታ ይገልፃል፡፡ሐይ ባይ በሌለበት እየተከታተሉ ገደል መግባት ሆኖአል፡፡ ወደ ቃሉ ብንመለስ ይበጃል፡፡
ሐይማኖትአለን፤ግን እየሞትን ነው፡፡አይሁድ የአብርሐም ልጆች፣የእግዚአብሔር ልጆች ነን እያሉ ይመፃደቁ ነበር፡፡ ጌታ ግን “እናንተ ከአባታችሁ ከዲያብሎስ ናችሁ” ይላቸው ነበር ዮሐ 8፡44፡፡ በሙሴ ሕግና በነቢያት መጽሐፍት ላይ የተመሰረተ ጥብቅ ሐይማኖት አለን ሲሉ የዲያሎስ ልጆች ሆነው ነበር፡፡ የሐሰተኛ ነቢያትም አስተዋፅኦ አለበት፡፡አሁንም ይህ ለኛ ማስጠንቀቂያ ነው፡፡መመለሱ ይበጀናል፡፡ ወደ ቃሉ፡፡
በራዕይ መጽሐፍ ምዕራፍ 2 ላይ የተጠቀሰችዋ የትያጥሮን ቤተ ክርስቲያን ሐሰተኛ ነብይ ኤልዛቤል ህዝቡን በማሳትና ለሰይጣን ጥልቅ ሚስጥር ተብዬ በማመቻቸት የተሳካላት ነበረች፡፡ ቢሆንም ጌታ ለእርሷና ለተከታዮቿ የንሰሐን ጊዜ እንደሰጠ ለእኛም ይሰጠናል፡፡ ስለዚህ እንደ ቃሉ ባልሆነ ትምህርትና አካሄድ ውስጥ ለጨመሩን ነብያትም ሆነ ለእኛ ለተከታዮቻቸው መመለስ ይበጀናል፡፡
ማሳሰቢያ
በዚህ ፅሁፍ ውስጥ ነብያት የተባሉት ከቀናው መንገድ የወጡትንና ሐሰተኞችን የተመለከተ መሆኑን መግለፅ ያስፈልጋል፡፡
Disciples of Jesus/Restoration
1bible.page.tl

No comments:

Post a Comment