Sunday, July 26, 2015

ጴንጤ Vs አይሁድ


ኢየሱስም ወደ ፊሊጶስ ቂሳሪያ አገር በደረሰ ጊዜ ደቀመዛሙርቱን ሰዎች የሰውን ልጅ ማን እንደሆነ ይሉታል? ብሎ ጠየቀ፡፡ እነርሱም፡- አንዳንዱ መጥምቁ ዮሐንስ ሌሎቹም ኤልያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው ይላሉ አሉት’’ ማቴ 16፡13-14፡፡
በአብዛኛው ሀዋርያት ከህዝቡ ያገኙት መረጃ የኢየሱስን ማንነት በአንድ የብሉይ ኪዳን ነቢይ ደረጃ የሚያስቀምጥ ነው፡፡ ለእነርሱ ጌታ ከአንድ የብሉይ ነቢይ የበለጠ ምንም አላደረገም፡፡ እንደውም ኤሊያስ ዝናብና እሳትን ለምኖ ከሰማይ ምልክት አሳይቶአል፡፡ ሙሴ ከሰማይ መና፡ ሳሙኤልም እንዲሁ ነጎድጓድና ዝናብ እንዲወርድ አድርገዋል፡፡
ጌታ ደቀመዛሙርቱን ህዝቡ ስለእርሱ ማንነት ያለውን ግንዛቤ በተመለከተ ጥያቄ እንዲጠይቅ ያደረገው በዚያው ማቴ 16፡1 ላይ ከፈሪሳውያንና ሰዱቃውያን ከሰማይ ምልክት እንዲያሳያቸው’’ የቀረበለት ልመና ነው፡፡ ከሰማይ ምልክት ካሳያቸው ከነሙሴ፣ ሳሙኤል፣ ኤልያስ ወዘተ… ጋር እኩል ሊያደርጉት፡፡
ሐዋርያቱ ጭምር ስለ ሰማሪያ ሰዎቸ ፡-‹ ጌታ ሆይ ኤልያስ ደግሞ እንዳደረገ እሳት ከሰማይ ወርዶ ያጥፋቸው እንል ዘንድ ትወዳለህን? › ብለውት ነበር ሉቃ 9፡54፡፡ ይህ የኤልያስ አገልግሎት በሐዋርያቱ ላይ ጭምር ተፅዕኖ አሳድሮአል ማለት ነው፡፡
ስለዚህ ጌታ እንዚህን ሰዎቸ / ያዕቆብን፣ ዮሐንስንና ጴጥሮስን/ ይዞ ወደ ረጅም ተራራ አወጣቸው፡፡ በፊታቸውም በመለወጥ ታላቅ ክብሩን አሳያቸው፡፡ ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ታዩአቸው፡፡ በጌታና በነሱ ክብር መካከል ምን ያህል ልዩነት እንዳለ ማስተዋል ነበረባቸው፣ ከመጭበርበር ይድኑ ዘንድ ማቴ 19፣1-8፡፡ ከዚያ ሲመለሱ የጠየቁት ጥያቄ ከነበረባቸው ጥያቄ ማረፋቸውን ያሳያል፡፡«እንግዲህ ፃፎች ኤልያስ አስቀድሞ ሊመጣ ይገባዋል ስለምን ይላሉ?» ማቴ 17፡10፡፡ ለዚህ ነው የእግዚአብሔር ቃል በ1ቆሮ 1፡22 ላይ «መቼም አይሁድ ምልክትን ይለምናሉ» የሚለው፡፡ ይህ ምልክት ናፋቂነት ከዳኑም በኋላ በብርቱ በጴንጤዎች ዘንድ የሚታይ ነገር ነው፡፡ ምልክት ያላመኑትን ወደ ጌታ ይስባል እውነት ነው፡፡ ጌታም በድንቅና ተአምራት የሐዋርያቱን ምስክርነት እውነትነት ያጸና ነበር፡፡ ታላቅ ስህተት የምንሳሳተው የጌታን ድንቅና ተአምራት ለትልቅነቱ መመዘኛ አድርገን የወሰድነው እንደሆነ ነው፡፡ምክንያቱም አዲስ ኪዳን ደግሞ ደጋግሞ እንደሚነግረን የሚታየውና የማይታየው ዓለም ሁሉ የተፈጠረው በእርሱ መሆኑን ነውና፡፡
ይህንን ትልቅ አምላክ በአይምሮ ሊገመት የማይችል ኃይል ባለቤት አንድ አይን ሲፈውስ፣ሽባ ሲተረትር፣ ኩላሊት ሲፈውስ ወዘተ አይቶ እና አሳይቶ ትልቅነቱን ለማወጅ መነሳት ትልቅ የመረዳት ችግር ነው፡፡ እርሱን ከብሉይ ዘመን ነቢያት ጋር ማጭበርበር ብቻ ሳይሆን ወደ ፊት ሊገለጥ ካለው ከሐሰተኛው ክርስቶስ ኃይል ጋርም ማምታታት ይሆናል፡፡
አጋንንት በስሙ ቢወጡ ለትልቅነቱ ማስረጃ አይሆንም፣ ነገር ግን ለሰው ልጆች ስላሳየው ምህረት ምልክቶች ናቸው፡፡ ደስታችንም አጋንንት በስሙ ስለተገዙልን ሳይሆን ምህረት ተደርጎልን በሰማያት ስማችን በመጻፉ ሊሆን እንደሚገባ ጌታ ራሱ ተናግሮአል ሉቃ 10፡20፡፡
ዮሐ 4 ላይ የተጠቀሰችው ሳምራዊት ሴት ጌታን፡-1. እንደ ተራ አይሁዳዊ ማለትም
መንገድ ሲሄድ የደከመው፣ ውሃ የጠማው፣ ከዚያ መቅጃ ስለሌለው ሊቀዳ የሚመጣ ሰው የሚጠብቅ አድርጋ ተረድታዋለች / ቁ. 9-11/፡፡ የገዛ አገሩ ሰዎችም፡-«ይህን ጥበብና ተአምራት ከወዴት አገኘው የጸራቢ ልጅ አይደለምን» እያሉ እንዲሁ ይረዱት ነበር ማቴ 13፡54፡፡
2. እንደ ነብይም ተረዳችው /ቁ.19/
ሌሎችም ፤- ያደረገውን ምልክት ባዩ ጊዜ ፤ «ይህ በእውነት ወደ ዓለም የሚመጣው ነቢይ ነው አሉ» ዮሐ 6፡14 ፡፡ ተከታዮቹም «በስራና በቃል ብርቱ ነብይ» ሲሉ ተናግረውለታል ሉቃ 24፡19፡፡
3. በመጨረሻም በመሲህነት ተረዳቸው /ቁ. 25/
ጴጥሮስም፡-« አንተ ክርስቶስ….ነህ» ብሎታል ማቴ 16፡16 ላይ፡፡ ለቆርኔሌዎስ ሲሰብክም እንዲሁ ፡- « እግዚአብሔር የናዝሬቱን ኢየሱስን በመንፈስ ቅዱስ በኃይልም ቀባው፣ እርሱም መልካም እያደረገ ለዲያብሎስም የተገዙትን ሁሉ እየፈወሰ ዞረ …. በእርሱ የሚያምን ሁሉ በስሙ የኃጢአትን ስርየት እንዲቀበል ነቢያት ሁሉ ይመሰክሩለታል» ብሎአል ሐዋ. 10፡38፣43፡፡
የብዙ አይሁዳውያን መረዳት ጌታ ተራ አይሁዳዊ ነብይ በመሆኑ ላይ የተገደበ ነው፡፡ ጥቂቶች ደግሞ መሲህነቱን ተቀብለዋል፡፡ እጅግ በጣም ጥቂቶች ደግሞ የእርሱን ማንነት ማለትም ፍፁም አምላክነቱን ተረድተዋል፡፡
4. ጥቂቶች ፍጹም አምላክ እንደሆነ ተረዱ /ዮሐ 20፡28/:
ዮሐ. 1፡1-3፣ ሮሜ 9፡5 ቲቶ 2፡13፣ 2 ጴጥ 1፡1፤1ዮሐ 5፡20
‹እርሱ እውነተኛ አምላክና የዘላለም ህይወት ነው › ይላል፡፡ ዓለማት
ሁሉ በእርሱ ተፈጥረዋል / ዕብ 1፡2/፡፡
ማጠቃለያ
አይሁዳውያን ለጌታ ታላቅነት ማስረጃ ለዚያውም ገና ከብሉይ ኪዳን ነቢያት ጋር የእኩያነት ደረጃ ሊያጎናጽፉት ከሰማይ ምልክት ከእርሱ ይጠይቁ ነበር፡፡ ጴንጤ ጋር ያለው ችግር ደግሞ የሚመነጨው ጌታ በመንፈስ ቅዱስ በኃይልም ተቀብቶ ያደረገውን ድንቅና ተአምራት ሲያሳድዱ ሳያውቁት አምላክነቱን መዘንጋታቸው ነው፡፡ አንድ አጋንንት በስንት እዝጊዎታ ሲጮህ “ጌታ ትልቅ ነው” ተብሎ እልልታውና ጭብጨባው ይቀልጣል፡፡ አንድ በሽተኛ ሲፈወስ ሰፈር በጩኸት ያናጋል፡፡ በመገለጥ የአንድ ሰው ስም የተጠራ እና አሁን እየሆነ እንዳለው ስልክ ቁጥሩ የተነገረ እንደሆነ አገር በእልልታ ይቀልጣል፡፡በየአውሊያው ቤት ይህ እኮ ቀላል ነገር ነው፡፡ ለመሆኑ የሚታየውንና የማታየውን አለም የፈጠረ ማነው?
ደስታው ጥሩ ፣ በጣም ጥሩ ነው፡፡ ግን ስለተደረገልን ምህረት እንጂ ስለጌታ ትልቅነት ከሆነ ስህተት ነው፡፡ “ለምን?” ሲባል ጌታ የፍጥረት ሁሉ ፈጣሪ፣ ባለቤትና ገዢ ስለሆነ በዚህች ትንሽ ምልክት ትልቅነቱ አይመዘንምና ፡፡ ስለዚህ የጌታን ማንነት በሚዛናዊነት ተረድቶ ተሀድሶን ከምልክቶችና ከተአምራቶች ጋር ብቻ በማያያዝ መሞቁና መቀዝቀዙ ቢቀር ለማለት ነው፡፡

1bible.page.tl 

No comments:

Post a Comment